• Call Us
  • +251..........

ዮ.. ዮ ..ጋሞ ማስቃላ

ዮ.. ዮ ..ጋሞ ማስቃላ 

‎የጋሞ ህዝብ የሰላም፣ የፍቅር እና የአንድነት መገለጫ የሆነው ዮዮ ማስቃላ የዘመን መለወጫ በዓል "ዱቡሻና ዱቡሻ ወጋ ለዘላቂ  ሰላማችን እና ልማታችን " በሚል መሪ ቃል ከመስከረም 10-12/2018 ዓ.ም ይከበራል።

‎በዓሉም በአርባምንጭ ከተማ በህዝቦች አብሮነት፣ አንድነትና በኅብረ-ብሔራዊነት ይበልጥ አሸብሮቆ በታላቅ ድምቀት ይከበራል!!   

‎በወርሃ መስከረም የሚከበረው የ' ዮ'  ጋሞ ማስቃላ ዘመን መለወጫ በዓል በጉጉት ተጠባቂና በሀገራችን ልዩ  ድባብ ከሚስተዋልባቸው በዓላት አንዱ ነው፡፡ 

‎በጋሞዎች  ‹ዮ '' ማስቀላ›  ማለት ‹መስቀል እንኳን ደህና መጣልን› ማለት ነው፡፡ የሕዝቡ የዘመን መለወጫ በመሆኑ በልዩ ድምቀትም ይከበራል፡፡ 

‎ለዮ ማስቃላ በዓል ሲባል እናቶችና አባቶች እቁብ በመጣል ዝግጅቱን ይጀምራሉ፡፡ 

‎እናቶች ለማስቃላ ቡላ፣ ወተት፣ ቂንጬ ለመሥራት የሚያገለግለውን ገብስ፣ በቆሎ፣ ቅቤና ቅመማ ቅመም ለማዘጋጀት ዓመቱን ሙሉ እቁብ ሲጥሉ ይከርማሉ፡፡ 

‎አባቶች ደግሞ የሚጥሉት እቁብ ለሰንጋ መግዣነት የሚውል ነው፡፡ 

‎ወጣቶች ለደመራ እንጨት በመሰብሰብና በማሰናዳት፣ ለከብቶች ሳር አጭዶ በመከመርና ጉልበት የሚጠይቁ ሥራዎች ላይ በመሳተፍ ያግዛሉ፡፡ 

‎"ዮ "ማስቃላ በጋሞ ብሔረሰብ በኩል ሁሉም ቂሙን ረስቶ በእርቅ፣ በይቅርታ፣ በሠላምና በአብሮነት ከክፉ ተግባርና ሐሳብ ወጥቶ በአዲስ መንፈስ የሚታደስበት ጊዜ ነው፡፡ 

‎የ"ዮ "ማስቀላ በዓል በጋሞዎች ምድር ረዘም ላለ ጊዜ ይዘልቃል፡፡ 

‎ዝግጅቱ ለሰዎች ብቻ ሳይሆን እንስሳትንም በማሰብ የሚከናወን ነው፡፡ በበዓሉ ወቅት ሁሉም ወደ በዓሉ የሚሄዱ በመሆኑ  ከብቶች የሚመገቡት ድርቆሽ ቀደም ብሎ ይዘጋጃል፡፡ ከዚህ ውጭ በበዓሉ ወቅት የሚግጡት ሰፊ ቦታ/ ካሎ/  ለግጦሽ ተካልሎ ይቀመጣል። 

‎ሕጻናት ከብቶቹን ወደ ግጦሽ መስክ ካሰማሩ በኋላ  ‹‹ለአዲሱ ዓመት እንኳን አደረሰን፤ እንኳን መስቀል በሰላም መጣልን፤… … በደስታ አደረሰን እያሉ ያከብራሉ ።